ናሽናል ኮንስትራክሽን ሪልስቴት የተመሠረተው በ2003 ዓ.ም. ነው፡፡ ላለፉት 13 ዓመታትም በተለይ ለቅይጥ አገልግሎት የሚውሉ ሕንፃዎችን ለደንበኞቹ በመሥራት ይታወቃል፡፡ ኢንጆይ ጀነራል ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበርና ዊ ኬር ሱፐር ማርኬት የናሽናል ኮንስትራክሽንና ሪል ስቴት እህት ድርጅቶች ናቸው፡፡ የድርጅቱ መሥራችና ዋና ዳይሬክተር አቶ ሙሉጌታ ዘለቀ ናቸው፡፡ በግንባታው ዘርፍ ያላቸውን አስተዋጽኦና ተያያዥ ጉዳዮችን አስመልክቶ አበበ ፍቅር አነጋግሯቸዋል፡፡
ሪፖርተር፡- የቤት ችግርን ለማቃለል እንደ ሪልስቴት አበርክቷችሁ ምንድነው?
አቶ ሙሉጌታ፡- የቤት ችግርን መንግሥት ብቻ የሚፈታው አይደለም፡፡ እያንዳንዱ ባለሀብት ምን ሠራሁ ብሎ ሊያስብ ይገባዋል፡፡ ችግሩን ለመፍታት ናሽናል ኮንስትራክሽንና ሪልስቴትን የመሰሉ ብዙ ሪልስቴቶች በከተማችን ይገኛሉ፡፡ ስለዚህ ሁላችንም ከመንግሥትና ከባንኮች ጋር በጥምረት በመሥራት ቤትን ለሁሉም ሰው ተደራሽ ማድረግ ይቻላል እላለሁ፡፡ በኛ በኩል ሪልስቴቶችን እየገነባና ለተጠቃሚዎች እያስተላለፍን ነው፡፡
ሪፖርተር፡- በእናንተ ድርጅትም ሆነ በአጠቃላይ በኮንስትራክሽን ዘርፍ ያለባችሁ ተግዳሮት ምንድነው?
አቶ ሙሉጌታ፡- እንደ ናሽናል ኮንስትራክሽንና ሪልስቴት ተግዳሮት የሆነብን የጥሬ ዕቃ አቅርቦት እጥረት ነው፡፡ አብዛኞቹ ጥሬ ዕቃዎች ከውጭ የሚገቡ መሆናቸው ችግሩን ያጎላዋል፡፡ መንግሥት ፋብሪካዎችና የኢንዱስትሪ መንደሮች በብዛት እንዲገነቡ ቢያደርግ ችግሩን ማቃለል ይቻላል፡፡ አሉሚኒየም፣ መስታወት፣ ብረትና ሴራሚክ በአገር ውስጥ እንዲመረቱ ቢያደርግም የተሻለ ይሆናል፡፡ ለዘርፉ ትልቁ ችግር ይኼ ነው፡፡ በሁለተኛ ደረጃ ለኮንስትራክሽኑ እንደፈተና ሊወሰድ የሚችለው የትምህርት ሥርዓቱ በተግባር ያልተደገፈ መሆኑ ነው፡፡ አብዛኛው የቀን ሠራተኛ በሙያ የበለፀገ አይደለም፡፡ የሚሠራውን ነገር ለይቶ አያውቅም፡፡ መስታወት ላይ ብሎኬት የሚጭን ሠራተኛ ነው ያለው፡፡ ይህ ደግሞ በእኛ ብቻ የሚፈታ ችግር ስላልሆነ የትምህርት ሥርዓቱ በተግባር የተደገፈ መሆን አለበት፡፡ የግንባታ ሠራተኞች የሚያስፈልገውን ክህሎት እንዲያሟሉ ትምህርታቸው በሥራ ላይ ልምምድ የታገዘ መሆን አለበት፡፡ ተማሪዎች የሚማሩትንና የሚሠሩትን አውቀው ቢወጡና የጠቀስኳቸው ችግሮች ቢቃለሉ የሪልስቴትን ችግር ለመፍታት ጠቃሚ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
ሪፖርተር፡- የመንግሥት ድጋፍ ምን መሆን አለበት ትላላችሁ?
አቶ ሙሉጌታ፡- ባለሀብት ከአገር ውጭም ኢንቨስት ማድረግ ይችላል፡፡ ነገር ግን በአገር ውስጥ ማልማት ትልቅ ፀጋ ነውና መንግሥት የተለያዩ ድጋፎችን ቢያደርግ ለምሳሌ የመሬትና የተለያዩ ጥሬ ዕቃዎች እንዲቀርቡ ቢያመቻች የተሻለ ነው፡፡ በቅርቡ የተጀመረ አርባ ሰላሳ የተባለ ለሪልስቴቶች የቀረበ ፕሮጀክት አለ፡፡ ይህ ደግሞ ለእኛ ጥሩ ጅማሮ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡
ሪፖርተር፡- በቀጣይ ምን ለመሥራት አስባችኋል?
አቶ ሙሉጌታ፡- በቀጣይ ሪልስቴት ብቻ ሳይሆን በተለያዩ የግንባታ ሥራዎች ለመግባት እናስባለን፡፡ ከተማን ማስዋብ ከእያንዳንዱ ባለሀብት የሚጠበቅ ሲሆን፣ እኛም በዚሁ ልክ አስተዋጽኦ ማበርከት እንዳለብን ይሰማኛል፡፡ በቀጣይም በመገናኛ አካባቢ ባለሦስት ቤዝመንት ግራውንድ ፕላስ 19 ሕንፃ ለመገንባት ወደ ሥራ የምንገባ ይሆናል፡፡
ሪፖርተር፡- የናሽናል ኮንስትራክሽን ሪልስቴት እህት ድርጅቶች ያላቸው እንቅስቃሴ ምን ይመስላል?
አቶ ሙሉጌታ፡- በብዛት የተሠማሩት በንግዱ ዘርፍ ነው፡፡ ለአብነትም ዊ ኬር ሱፐርማርኬት ከ25 በላይ ሠራተኞችን የያዘ ነው፡፡ ኢንጆይ ጀነራል ትሬዲንግ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ሌላኛው እህት ድርጅት ነው፡፡ በሴራሚክና ፈርኒቸር አስመጭነት እየተሳተፈ ይገኛል፡፡ የግንባታ ማጠናቀቂያ ዕቃዎችን በማስመጣት ዘርፍ እየሠራ ነው፡፡ ከቅርብ ጊዜ ወዲህም የሥራ ዘርፍን በማስፋፋት የእርሻ መሬቶችን በመውሰድ በግብርናና ከብት በማደለብ ሥራ ተሠማርቷል፡፡ በተጨማሪ ፋብሪካ በመገንባትና የኢንዱስትሪ ማዕድናት በማምረት ለመሠማራት የዝግጅት ሥራውን በማጠናቀቅ ላይ ይገኛል፡፡
ሪፖርተር፡- የካቪው የሚባል ሪልስቴት አስመርቃችኋል፡፡ ስለእሱ ቢገልጹልን?
አቶ ሙሉጌታ፡- የካቪው የተባለው የመኖሪያ ቤት በናሽናል ኮንስትራክሽንና ሪልስቴት የተገነባ አፓርትመንት ነው፡፡ ያለውን የገበያ ግሽበት ተቋቁመን ያለምንም ጭማሪ ለተገልጋዮቻችን አስረክበናል፡፡ ሌሎች ሪልስቴቶች የእኛን ተሞክሮ ቢወስዱ ተጠቃሚ ይሆናሉ ባይ ነኝ፡፡ ኢንተርፕሩነር መሆን አንዱ ጠቀሜታው ለማኅበረሰቡ አስፈላጊውን አገልግሎት መስጠት ማስቻሉ ነው፡፡ ቤቶቹ እንዲሁ ቤት ብቻ ሳይሆኑ ትክክለኛ መኖሪያ ቤቶች ናቸው፡፡ ከፍታቸው ከሦስት ሜትር በላይ ሲሆኑ፣ 80 ካሬ የሆኑ ባለ ሦስት መኝታ ቤቶች አሉት፡፡ እያንዳንዱ ቤት ለኑሮ ምቹ የሆኑና የየካን ተራራ የሚያሳዩ ቤቶች ናቸው፡፡ 155 ካሬ ስፋት ያላቸው ባለሁለት መኝታ ቅንጡ ቤቶችም አሉት፡፡