[ad_1]
ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia
[ክቡር ሚኒስትሩ እየጠራ ያለውን የእጅ ስልካቸውን ተመለከቱና ደዋዩ አንድ ወዳጃቸው ባለሀብት መሆናቸውን ሲያውቁ አነሱት]
- ጤና ይስጥልኝ ክቡር ሚኒስትር?
- እንዴት ነህ ወዳጄ?
- ሰሞኑን በተደጋጋሚ ብደውልም ስልኩ ከአገልግሎት መስጫ ክልል ውጪ ናቸው እያለ አስቸገረኝ።
- አዎ፣ ወጣ ብዬ ነበር።
- ከአገር ውጭ ነበሩ?
- አይ… እዚሁ ነው።
- ምነው በሰላም?
- በሰላም ነው፣ የካቢኔ አባላት አንድ ላይ ሆነን የተለያዩ አካባቢዎች ጉብኝት እያደረግን ነበር።
- አዎ… እርስዎም እዚያ ነበሩ እንዴ ክቡር ሚኒስትር?
- የት ማለትህ ነው?
- ፍለጋ መሰለኝ፣ ብቻ በቴሌቪዥን ተመልክቼ ነበር።
- ምን ፍለጋ?
- ያው አንድ በጫካ የተከበበ ወንዝ ነዋ የሚሆነው።
- ለምን? ምን ያደርግልናል?
- ለማስፋፋት አስባችሁ መሰለኝ።
- ምኑን?
- ፕሮጀክቱን።
- የትኛውን ፕሮጀክት?
- የገበታውን ነዋ፡፡
- የምን ገበታ ነው የምትለው?
- አንዴ ለአገር አንዴ ለትውልድ የምትሉትን ገበታ ማለቴ ነው።
- እህ… ገባኝ ገባኝ፣ የጉብኝቱ ዋና ዓላማው ለዚያ ባይሆንም አንድ ቦታ ግን አግኝተናል።
- የፈራሁት ሊመጣ ነው ክቡር ሚኒስትር?
- ምንድነው የምትፈራው?
- አዋጡ የምትሉትን ነዋ ክቡር ሚኒስትር።
- ለምንድን ነው የምትፈራው? ለአገር የሚደረግ አስተዋጽኦ አይደል እንዴ?
- ቢሆንም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እንዴት?
- ምክንያቱም እኛ እናዋጣለን እንጂ ከገበታው ተቋድሰን አናውቅም፡፡
- አልገባኝም?
- እኛ እናዋጠላን፣ ከገበታው የሚበሉት ግን ሌሎች ናቸዋ።
- እንዴት?
- እኔ ለገበታ አዋጣ በተባልኩ ቁጥር አዋጣለሁ።
- እሺ?
- የጀመርኩትን ፕሮጀክት ለማስፋፋት ላቀረብኩት የመሬት ጥያቄ ግን መልስ የሚሰጠኝ አላገኘሁም፣ ከእኔ በኋላ ጥያቄ ያቀረቡ ሌሎች ባለሀብቶች ግን ያለ ችግር ያገኛሉ።
- አንተስ ለገበታ አዋጥቻለሁ ብለህ ብቻ መሬት ትጠይቃለህ እንዴ?
- ሌላ ምን ማድረግ ነበረብኝ ክቡር ሚኒስትር?
- ቢያንስ ለአንድ ሚኒስትር ሌላ ተጨማሪ ነገር ማድረግ ነበረብህ።
- ምን ክቡር ሚኒስትር?
- ሚኒስትሩ የሚያስገነባውን ሕንፃ ማገዝ ሊሆን ይችላል ወይም ሌላ ነገር።
- ሌላ ነገር ምን?
- እሱ እንደምትመርጠው ሚኒስትር ይለያያል።
- ስለዚህ አለብኝ ማለት ነዋ?
- ምን?
- ሌላ ገበታ።
- የምን ገበታ?
- ገበታ ለሚኒስትር!
[ክቡር ሚኒስትሩ ከሚያከብሯቸው አንድ የቀድሞ ጉምቱ ፖለቲከኛ ስልክ ተደውሎላቸው እያወሩ ነው]
- አንዳንድ ነገሮች ቢያሳስቡኝ ነው ቀጠሮ ሳልይዝ ላናግርዎት የፈለግኩት ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እርስዎማ ቀጠሮ መያዝ አያስፈልግዎትም፣ ምን ገጠመዎት?
- እኔማ ምን ይገጥመኛል እርስዎን ልጠይቅዎት እንጂ?
- ምን?
- እውነት ለመናገር የማየው ነገር አሳስቦኛል፡፡
- ይንገሩኝ ምንድነው ያሳሰበዎት?
- ሌት ተቀን የሚሠራው ነጋዴ እየከሰረ ነው።
- መቼም የውጭ ኃይሎች የፈጠሩብንን ችግር ያውቁታል።
- ከእሱ ጋር አይገናኝም ክቡር ሚኒስትር፡፡
- እንዴት?
- ሌት ተቀን የሚሠራ ታታሪ ነጋዴ ችግር እሱ አይደለም።
- ምንድነው?
- ታታሪ ነጋዴ እየመነመነ ሳለ በተቃራኒው ግን ሌላ…
- በተቃራኒው ምን?
- መሽቶ ሲነጋ ሀብት አፍርተው የሚታዩ ሰዎች እንደ አሸን እየፈሉ ነው።
- ምን ማለትዎ ነው?
- ጠንክሮ መሥራት ሀብት የሚፈጠርበት መንገድ መሆኑ ቀርቶ ሌላ ዓውድ ተፈጥሯል እያልኩ ነው።
- የምን ዓውድ?
- ሲነጋ ሀብታም መሆን የሚቻልበት ዓውድ።
- አልገባኝም?
- ምነው ክቡር ሚኒስትር?
- ምነው?
- ሁሉን ነገር አስረዳ እያሉኝ እኮ ነው።
- እውነት አልገባኝም? እንዴት ያለ ዓውድ ነው በብርሃን ፍጥነት ሀብት የሚያስገኘው?
- አልገባኝም ካሉማ እነግርዎታለሁ።
- ይንገሩኝ፡፡
- ሲነጋ ሀብት የሚፈጠርበት ሥልት አንድና አንድ ነው።
- ምንድነው?
- ከከፍተኛ ባለሥልጣን ጋር ግንኙነት የመፍጠር ሥልት ነው፣ ወንድም ወይም ዘመድ አዝማድ የመሆን ሥልት፡፡
- እሱን ነው እንዴ? ይህንንማ እኛም ገምግመናል።
- ምን ብላችሁ ገመገማችሁት?
- በዝተዋል ብለን ገምግመናል።
- እነማን ናቸው የበዙት?
- አካም አካም የሚሉ!
The post [ክቡር ሚኒስትሩ እየጠራ ያለውን የእጅ ስልካቸውን ተመለከቱና ደዋዩ አንድ ወዳጃቸው ባለሀብት መሆናቸውን ሲያውቁ አነሱት] first appear on ሪፖርተር – Ethiopian Reporter – #1 Best and reliable news source in Ethiopia and is written by በጋዜጣዉ ሪፓርተር
[ad_2]
Source link