በሰለሞን ኃይለ ማርያም
ባለቤቴ ኃይለኛ ነች፡፡ እኔም ስናደድ ከባለቤቴ የተሻልኩ አይደለሁም፡፡ ባለቤት ስትናደድ ባገኘው ነገር ልጃችንን መማታት ይቀናታል፡፡ ታዲያ አንድ ቀን ልጃችን ከትምህርት ቤት ጓደኛው ጋር ሲጨዋወት ‹‹እናቴ ስትቆጣ ትማታለች ኃይለኛ ነች ይለዋል›› ጓደኛውም እንደዋዛ ‹‹አንተን ትማታለች?›› ‹‹አዎ›› ይላል የእኔ ልጅ፡፡ የልጄ ጓደኛ ለመምህሩ፣ መምህሩ ለርዕሰ መምህሩ፣ ርዕሰ መምህሩ የልጆች ጉዳይን ለሚመለከት የመንግሥት ተቋም ሪፖርት ያደርጋል፡፡ ከመንግሥት መሥሪያ ቤት ለባለቤቴም ስልክ ተደውሎ ‹‹ልጃችሁን እንደምትማቱ ተረድተናል፣ በልጁ አካል ላይ ምንም የድብደባ ምልክት የለም፣ በዚህ የተነሳ ጉዳዩን ወደ ሕግ አንወስደውም፡፡ ነገር ግን አሁን የደወልነው እንደ ማስጠንቀቂያ እንዲታይ፣ አሁን የተነጋገርነውን በኢሜይል እንልክላችኋለን እንደደረሳችሁ አሳውቁን፤›› ብለው ነገሩን፡፡ አስደንጋጭ የስልክ ንግግር ነበር፡፡
ርዕሰ መምህሩ እኛን መጀመርያ ሳያናግረን ቀጥታ ለመንግሥት አካል በማሳወቁ ቅር ብሎኝ ደውሎ ለምን መጀመርያ እኛን እንዳላናገረን ጠየቅሁት፡፡ ‹‹በአገሪቱ ሕግ መሠረት አንድ ልጅ በወላጆቹ ተመታሁ ካለ ወላጆቹን የማሳወቅ ኃላፊነት የለብንም፡፡ ኃላፊነታችን በቀጥታ ለሚመለከተው አካል ማሳወቅ ነው፣ ይህንኑ አድርጌአለሁ፡፡ ይህንን ባላሳውቅ እኔ በሕግ እጠየቃለሁ፤›› አለ፡፡
በሌላ በኩል ደግሞ መንግሥት ለመጪው ትውልድ፣ ለሕፃናት፣ ለተማሪዎች ምን ያህል እንደሚቆረቆር፣ እንዴት እንደሚያስብና እንዴት እንደሚጠብቅ የሚያሳይ ነው፡፡
በእኛ አገርስ ልጆች ይጠበቃሉ? መንግሥት ተማሪዎችንና ሕፃናትን የሚጠብቅበት አሠራር አለው? መደባደብ፣ አካላዊ ቅጣት፣ ልጆች ላይ መጮህ፣ ልጆችን መግረፍ፣ በቤተሰብ በማኅበረሰብ እንዴት ይታያል? ልጆች ላይ በወላጆችና በመምህራን አካላዊ ቅጣት ማሳረፍ በልጆቹ አስተዳደግ ላይ፣ በልጆቹ የወደፊት ባህሪይ ላይ ምን ሊያመጣ ይችላል? ይህ የቅጣት ዘዴ እንደ አገር ወደፊት ምን ሊያስከትልብን ይችላል? ልጆችን መግረፍ፣ አካላዊ ቅጣት መፈጸም፣ መሳደብ፣ ኃይል ቃል መናገርና ልጆችን በኃይል የምንፈልገውን ነገር እንዲያደርጉ ማድረግ፣ ወዘተ ይህ የስልክ መልዕክት ከመጣ በኋላ ከባለቤቴ ጋር ልጃችንን መማታት ቀርቶ ላለመቆጣት ላለመጮህ ተስማማን፡፡ ‹‹እባክሽን ንዴትሽን ተቋቋሚ፣ አትጩሂበት፣ አትማቺ›› በማለት ባለቤቴን ሳግባባት ‹‹አይሰማም፣ ብነግረው፣ ብመክረው አይሰማም ስጮህና ስማታ ብቻ ነው የሚሰማኝ፤›› አለች፡፡
እንግዲህ ልብ በሉ ባለቤቴ በጣም ስትናደድ ልጃችን ሥርዓት እንዲይዝ የምትማታ ከሆነ ልጃችን ከዚህ ሁኔታ የሚመረው ምንድነው? ምናልባት ልጃችንም በጣም ሲናደድ መጀመርያ ትምህርት ቤት ጓደኞቹን ይማታ ይሆናል፡፡ አድጎ ትልቅ ሲሆን ደግሞ ምን ሊያደርግ ይችላል? አንድ ሰው መጀመርያ ትምህርት የሚማረው ከአባትና እናቱ ነው፡፡ ከፍ ሲል ደግሞ ከመምህራኖቹ፣ ከዕድሜ ጓደኞቹ ይማራል፡፡
በአገራችን የተጻፉ አብዛኞቹን የግል የሕይወት ታሪኮች ወይም ኦቶ ባዮግራፊ የማንበብ ዕድል አጋጥሞኛል፡፡ ብዙዎቹ የኦቶ ባዮግራፊ ጸሐፊዎች ደግሞ ትልቅ ደረጃ የደረሱ፣ የተማሩ ታዋቂ ሰዎች ናቸው፡፡ ሁሉም ማለት ይቻላል በልጅነታቸው ተገርፈዋል፣ ኃይለኞች ነበሩ፣ ቢያንስ ሲገረፉ አይተዋል፡፡ በአጠቃላይ አካላዊ ቅጣት ኢትዮጵያ ውስጥ የተለመደ፣ የነበረና አሁንም ያልጠፋ ጉዳይ ነው፡፡
በጣም የሚገርመው ደግሞ እዚህ የምኖርበት ካናዳ ሕፃናት በፍፁም አካላዊ ቅጣት አይደርስባቸውም፡፡ ሌላ ቀርቶ ድምፅን ከፍ አድርጎ ልጅን መቆጣት እንደ ነውር የሚታይበት አገር ነው፡፡ ታዲያ ልጆቹ ሁሉም ማለት ይቻላል ሥነ ሥርዓት ያላቸው፣ በራሳቸው የሚተማመኑ፣ ንቁና ብሩህ ናቸው፡፡ ሚስጥሩ ምንድነው? እኛ ተጋርፈንም፣ ጮኸንም የምናሳድጋቸው ልጆች በአካላቸውም ሆነ በአዕምሯቸው ጠባሳ ይዘው፣ ሽቁጥቁጥ፣ ቂመኛና ተወያይቶ የማሳመን፣ ሰጥቶ የመቀበል፣ የመደራደርና የመነጋገር ባህል የሌላቸው የመሆን ዕድል ይዘው ያድጋሉ፡፡ እዚህ ተልደው ያደጉ ልጆች ግን ንፁህ አዕምሮ ይዘው፣ ችግር ሲገጥማቸው ተደራድረው፣ ተወያይተው፣ ወይም ሰጥተው በመበል በሰላም ችግራቸውን ይፈታሉ፡፡ ይህ እንግዲህ ያስተዋልኩት፣ የታዘብኩትና ያሰላሰልኩት ነው፡፡
በቅርቡ የዶክትሬት ትምህርቴን ስከታተል ይህንኑ በልጅነት የመገረፍ/የመቀጣት ጉዳይ አንስቼ ከኢትዮጵያ የፖለቲካ ባህል ጋር ይገናኝ እንደሆነ ለመመርመር በምሞክርበት ወቅት፣ ምርምሩን የምትከታተለው ፕሮፌሰር ይህ ጉዳይ ራሱን ችሎ ሰፊ ምርመራ የሚጠይቅ ነው በማለቷ ለጊዜው ጉዳዩን ወደ ጎን ትቼ ነበር፡፡ ይሁንና ይህ ጉዳይ እየተመላለሰ በአዕምሮዬ ስለሚመጣ እስኪ ለሪፖርተር አንባብያን ላካፍል በማለት ይህንን ጽሑፍ አዘጋጀሁ፡፡
በልጅነት መደብደብ፣ መገረፍ፣ መቀጣት ከኢትዮጵያ የፖለቲካ ባህል ጋር ዝምድና ይኑረው፣ አይኑረው ፕሮፌሰሯ እንዳለችው ሰፊ ጥናት የሚጠይቅ ነው፡፡ አሁን አንድ ግልጽ የሆነው ነገር ወላጆች ልጆቻቸውን ሲገርፉ፣ ሲማቱ፣ ሲቀጡ ለልጆቻቸው በተግባር እያስተማሩ ያለው ስትናደድ፣ ስትቆጣ፣ ስሜትህን መቆጣጠር ሳትችል ተጋረፍ፣ ተማታ፣ አካላዊ ጥቃት አድርስ እንደ ማለት ይቆጠራል፡፡ የሥነ ልቦና ባለሙያዎች በዚህ ጉዳይ የበለጠ እንደሚያስረዱ ምንም ጥርጥር የለኝም፡፡ አንድን ሕፃን የቤት ሥራ አልሠራህም፣ አጥፍተሃል፣ የሠራኸው ሥራ ልክ አይደለም ብለን የምንገርፈው ከሆነ፣ የምንቀጠቅጠው ከሆነ፣ የምንሰድበው፣ የምንጮህበትና የምናሸማቅቀው ከሆነ ይህ ልጅ ሲያድግ ምናልባትም የፖለቲካ ሥልጣን ሲይዝ ሌሎችን አጥፍተዋል ብሎ ቢገድል፣ ቢያስር፣ ቢደበድብ፣ ቢሳደብ፣ ሰዎችን ቢያሸማቅቅ ወይም አመፀኛ፣ አምባገነን ቢሆን ማነው ተጠያቂው? መደራደር፣ መወያየት፣ ሰጥቶ መቀበል፣ መነጋገርና ችግርን መፍታት በትምህርት ቤት፣ በቤት፣ ከአባትና ከእናት ልጆች ካልተማሩ ከየት ያመጡታል?
አስተማሪ፣ ወላጅ፣ አሳዳጊ ልጆች አጠፉ፣ ሥነ ሥርዓት እንዲይዙ እየተባለ ሲገርፉ፣ አካለ ጎዶሎ ሲያደርጉ፣ ዓይን ሲያጠፉ ከዚህም አልፎ ልጆች እንደሞቱ ተጨባጭ ማስረጃዎች አሉ፡፡ ልጆች የሚማሩት ኃይለኝነትን፣ መጋረፍን፣ መጮህን፣ በአጠቃላይ አምባገነንነትን ነው፡፡ ታዲያ መደራደር፣ መወያየት ሰጥቶ መቀበል ከየት ይምጣ?
ሴቭ ዘ ችልድረን የተባለ በኢትዮጵያ የሚንቀሳቀስ መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት እ.ኤ.አ. በ2011 ባሳተመው ሪፖርት በኢትዮጵያ ‹‹አካላዊ ቅጣትና ሕፃናትን ማዋረድ የተመደና ማኅበረሰቡ የተቀበለው ድርጊት እንደሆነ ዘግቧል፡፡ እኔም ባደረግሁት ጥናት አካላዊ ቅጣት በቤተሰብ ውስጥም ሆነ በትምህርት ቤት የተለመደ መሆኑን አመላካች መረጃ አግኝቻለሁ፡፡ በቅርቡ የታተመው የፕሮፌሰር ባህሩ ዘውዴን የግል የሕይወት ታሪክን (ኦቶ ባዮግራፊ)ን ጨምሮ ሁሉም የግል የሕይወት ታሪክ መጻሕፍት መገረፍንና መደብደብን እንደ ቀልድና እንደ ዋዛ ከትበውታል፡፡ አንዳቸውም ይህ በልጅነትቸው የደሰባቸው ግርፋትና ቅጣት በትልቅነታቸው ወቅት ያለውን ተፅዕኖ ሲጠቅሱ አይሰሙም፣ ወይም አልጠቀሱም፡፡
ሴቭ ዘ ቺልድረን ስዊድን እ.ኤ.አ. በ2008 ባደረገው ጥናት ተደጋጋሚ አካላዊ ቅጣት፣ በልጅነት የደረሰ ግርፋት፣ ስድብ፣ የማዋረድ ተግባር ማኅበረሰቡ አመፅን፣ ኃይለኝነትን ወይም ነውጥን እንደተቀበለ የሚያሳይ ነው ይልና ልጆች አድገው ትልቅ በሚሆኑበት ወቅት አመፀኛ፣ ተደባዳቢ፣ በንግግር የማያምኑ፣ ኃይለኛና ነውጠኛ ይሆናሉ ሲል ይደመድማል፡፡
‹‹ባለጌ ልጅን ካሳደገ የገደለ ይፀድቃል›› ከሚለው የተሳሳተ አደገኛ ብሂል ጀምሮ፣ ብዙ የሃይማኖት አስተሳሰቦች ጭምር ቅጣትን የሚያበረታቱ በመሆኑና በአገራችንም ሃይማኖት ታላቅ ተፅዕኖ ስላለው መቅጣት የሚበረታታበት ማኅበረሰብ የበዛበት አገር ነው ያለን፡፡
ይህንን አጭር ጽሑፍ ያዘጋጀሁት ሁሉም ሰው ስለውይይት፣ ስለድርድር፣ ስለሰጥቶ መቀበልና ስለመነጋገር ሲናገር ይደመጣል፡፡ ይህ መልካም ነው፣ ነገር ግን የሚነጋገር፣ የሚወያይ፣ ሰጥቶ የሚቀበል ማኅበረሰብ አለን ወይ ብሎ መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ አሁንም ቢሆን አልረፈደም፡፡ ልጆቻችንን በፍቅር፣ በመወያየት፣ በመነጋገር፣ ሰጥቶ በመቀበል የማሳደጉ ሒደት ዛሬውኑ መጀመር አለበት፡፡ ቢያንስ የአሁኑን ትውልድ እናትርፍ መጪውን ዘመን የተሻለ ለማድረግ ዛሬ ወላጆች፣ መምህራን፣ አሳዳጊዎች ትልቅ ኃላፊነት አለብን፡፡ ይህንን ጽሑፍ የሚያነቡ ወላጆች፣ መምህራንና አሳዳጊዎች የተሻለ ተግባር እንዲፈጽሙ ቢቻል፣ እንዲሁም በጽሑፍ ሐሳብን ማጋራት ቢቻል ለተጨማሪ ውይይትና መትፍሔ በር ቢከፈት መልካም ይሆናል፡፡
ከአዘጋጁ፡- ጽሑፉ የጸሐፊውን አመለካከት ብቻ የሚያንፀባርቅ መሆኑን እንገልጻለን፡፡